Description
ገሊላ Gelila by Tigist Wolde
ገሊላ በወጣትነት እና ቁንጅና ላይ እርጋታን የተላበሰች የአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ መምህርት ከዕለታት በአንዱ ቀን አንድ ድንገተኛ የስልክ ጥሪ ካልጠበቀችው ቦታ ይደርሳታል – ከአማኑኤል ሆስፒታል ። ደዋዩ በታታሪነትና በብሩህ አዕምሮው የምታውቀው አንድ ተማሪዋ ድንገተኛ የአዕምሮ ህመም እንደገጠመው እና በሆስፒታሉ የህክምና እርዳታ እየተደረገለት እንዳለ ፥ በአዕምሮ መታወክ ውስጥ ሆኖ ከሚጠራቸው ቦታዎችና ሰዎች ስም መካከል አንዷ እሷ መሆኗን ገልፆ ምንአልባት ልትጎበኘው ትችል እንደሆን ይጠይቃታል ።
ገሊላ ይህ ድንገተኛ የስልክ ጥሪ እና አሳዛኝ ክስተት ልቧን ነክቷት በአዕምሮ ህመም የሚሰቃየውን ተማሪዋን ለመጠየቅ በቅንነት መሄዷ ፈፅሞ ካልጠበቀችው ውስብስብ ታሪክና ለሷ ለራሷ እንኳ ፈፅሞ እንግዳ ከሆነባት ማንነቷ ጋር እንደሚያገናኛት ፈፅማ አልገመተችም ። ክስተቱ የፈጠረውን የተጠላለፈ የታሪክ ሰበዞች እንደ ፍንጭነት በመጠቀም ስትመረምር መላው ዓለም በጥብቅ የሚፈልገው የሰማያትን እና የምድርን ሚስጥራት የያዘ ፥ በሁሉም አጥናፍ ያሉ ፍጥረታትን እና ኃይላትን መቆጣጠር እና መግዛት የሚያስችል የንጉስ ሰለሞን የጥበብና የኃይል ምንጭ የሆነ ምስጢራዊና ምትኃታዊ መፅሀፍ ከሷ ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት እንዳለውና ይህን መፅሀፍ በሚስጥር ተደራጅቶ ከኢትዮጵያ ለመስረቅ እየታገለ ካለ ጠንካራ ቡድን ጋር ፊትለፊት ያጋፈጣት መሆኑን ትረዳለች …
* **
ገሊላ መፅሀፍ በመቼት ደረጃ ከእንግሊዝ እስከ አዲስ አበባ ፥ ከእንጦጦ ማርያም ቤተክርስትያን እስከ ወልድያ እና ግሸን ፥ ከደቡብ አፍሪካ እስከ ኮፐንሀገን ይሸፍናል ። በልብወለድ የዘውግ ምድብ (genre) ደረጃም የተወሳሰበ ምስጢርን መፍታት ላይ ያተኮረ ምስጢራዊ ልብወለድ (Mystrey Novel) ይመደባል ።
በዚህ በ 202 ገፆች የተሰናዳ ታሪክ ውስጥ ደራሲዋ ትዕግስት ወልዴ ውስብስብ የታሪክ አወቃቀር (Complex plot) መስራትን ችላበታለች ። በሳል የቋንቋ አጠቃቀም እና ገላጭ የሆነ ገፀባህሪ አሳሳል ችሎታዋም በጉልህ ይታያል ። እንደዚህ አይነት የማወቅ ጉጉትን የሚያጭር እና ሀገራዊ ጭብጥ ያላቸው መፅሀፍት በአብዛኛው አንባቢ ዘንድ እንደ በረከት የሚቆጠሩ በመሆናቸው የማንበብ ፍቅር ያለው አንባቢ ሁሉ ሊያነበው እንደሚገባ እጠቁማለሁ ።
[ፀኃፊ ሙላት ኪዳኔ ፥ በድሬዳዋ ዩንቨርስቲ የእንግሊዘኛ ስነፅሁፍ መምህር ]
Reviews (0)
You must be logged in to post a review.





Reviews
There are no reviews yet.